ከጊዜ ወደ ጊዜ የማህበራዊ ሚዲያ እና የማያቋርጥ የመረጃ ፍሰተ-ዓለም ውስጥ፣ በግርግሩ መካከል ጸጥታን መፈለግ ይበልጥ አስፈላጊ እየሆነ ነው። ኢትዮጵያውያን ወጣቶች ከቡድሂዝም “ሳቲ” ከሚለው ጽንሰ-ሀሳብ ብዙ የሚማሩት ነገር ያለ ይመስለኛል፤ “ሳቲ” የአዕምሮዓችንን ትኩረት አሁን ወዳለንበት ቅጽበተ-ዓለም የመምራት ልምድ ነው።
የንቃተ ህሊና/ጥሞና ጽንሰ-ሀሳብ
ምዕራባዊያን ይህንን አስተሳሰብ ትርጓሜ ብዙውን ጊዜ ‘ራስን ማስታወስ’ ወይም ‘ራስ ላይ ማንጸባረቅ’ አድርገው ይወስዱታል። ምዕራባዊያንን ያሉበትን ነባራዎ የመንፈሳዊ፣ ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ አዝቅት ከግምት ስናስገባ፤ ይህ ራስ ላይ የበዛ ትኩረት የማድረግ፤ከሪር ራስ ወዳድነት (Individualism/Egoism) አባዜ የሚገርም አይደለም። ይልቁንም ይህ የሚያመለክተው የኢንዱስትሪው ርዕዮተ ዓለም እንዲሁም ተከትሎት የመጣው የካፒታሊዝም ሪዮት ያስከተለውን የመንፈሳዊነት ኪሳራ እና የዘመናዊ ኑሮ ውጥረት የሚያስከትለው ሁኔታዎችን ለመቋቋም ምዕራባዊኑ ያላቸው ብቻኛ ፓራስታሞል መንፈሳዊነት መሆኑን ነው።
ነገር ግን ይህ የ”ሳቲ” ጽንሰ-ሀሳብ ከጂኦግራፊያዊ እና ከባህላዊ ድንበሮች የሚያልፍ እና በክርስትና እምነት ቀኖና እንዲሁም በእስልምና አቂዳ (Doctrine or Dogma) ውስጥም መስረታዊ አስተምሮት ሆኖ አግኝቼዋለው።
በቡድሂዝም ውስጥ፣ ‘ሳቲ’ በባህሪው የቅዱሳት ጽሑፎች እና ትምህርቶች ትውስታ የሚል ትርጓሜ ነው ያለው። ‘ሳቲ’ እንደ ኮምፓስ ሆኖ የሚያገለግል፣ በሕይወት ጉዟቸው ላይ የሚሠሩትን የሚ፟መራ፣ ከመንገድ ርቀው እንዳይሄዱ የሚከለክላቸው፣ ትኩረት የሚከፋፍሉ ነገሮች ውስጥ ገብተው እንዳይከርሙ የማድረግ ልምምድ ነው።
በእስልምና ‘ዚኪር’ በመባል የሚታወቀው ተግባር ከ‘ሳቲ’ ጋር ተመሳሳይነት አለው። ዚኪር ቀኑን ሙሉ አላህን የማስታወስ እና የማወደስ፣ በአእምሮ ውስጥ አላህን በባህሪያቶቹ ለማወቅ እንዲሁም አማኞች ከዱንያ ህይወት መጠላለፍ ልባቸውን እና አእምሮአቸውን ለማጥራት የሚደረግ ኢስላማዊ ተግባር ነው። ።
በክርስትና ውስጥ፣ እንደ ቡድሂዝም የሳቲ ፅንሰ-ሀሳብ ያለንን ትኩረት እና ጥንካሬ እንዲሁም ራስን የመወሰን ልክ (Devotion) ለእግዚአብሔር መስጠት ሆኖ ይገለጻል። እግዚአብሔርን በአስተሳሰባቸውና በድርጊታቸው ግንባር ቀደም ለማድረግ በመፈለግ ክርስቲያኖች ይህንን በጸሎት፣ በማሰላሰል እና በአምልኮ ተግባራዊ ያደርጋሉ፣ እንዲህ ዓይነቱ ራስን ለፈጣሪ መስጠት፤ ትኩረትን ከሚከፋፍሉ ነገሮች ርቆ ወደ መጨረሻው እውነታ የሚዞርበትን የሳቲ ሀሳብን ያንጸባርቃል።
የጥሞና ተቃራኒ: ’’ትኩረት መበተን’’
የንቃተ ህሊና ወይም ጥሞና ቀዳሚ ተቃዋሚ ’’ትኩረት መበተን’’ ነው። ይህ የትኩረት መበተን፣ ራሱን በሁለት የተለያዩ ግን እርስ በርስ በተያያዙ ቅርጾች ይገለጻል።
የመጀመሪያው የሚያመለክተው ውስጣዊ የግራ መጋባት ሁኔታን ነው – ግለሰቦች ከውስጣዊ ማንነታቸው እና አላማቸው ጋር ግንኙነት ሲያጡ፤ በሕልውና ውስጥ ካሉ ቀውሶች ጋር ሲታገሉ፣ በዓለም ላይ ባላቸው ቦታ ግራ ሲጋቡ የሚፈጠር ውስጣዊ ሁኔታ ነው።ይህ ከመንፈሳዊ ሥሮቻቸው የተፋቱ ግለሰቦች የዘለቀ ምሳሌ ነው። ይህ ውዥንብር ሲከርም ወደ አእምሮ ጭንቀት የሚያመራ እና የአንድን ሰው ስሜታዊ ደህንነት የሚያበላሽ ነው።
ሁለተኛው የ’’ትኩረት መበተን’’ ውጫዊ ነው, የግለሰቦችን ትኩረት አቅጣጫ ለማስቀየር የሚተጉ ኃይሎች ይገለጻል። ለምሳሌ የድርጅቶች ማስታወቂያ በኢንግሊዘኛ ’’Advert-isement” ተብሎ ይታወቃል፤ ትርጉሙም ” አቅጣጫ ማስቀየር” ማለት ነው። እነዚህ አካላት የግለሰቦችን ትኩረት ወደ ምርታቸው፣ አገልግሎታቸው ወይም ርዕዮተ ዓለማቸው ለማዞር ይጥራሉ ። ማህበራዊ ሚዲያዎችም፣ ይህን የማዘናጋት አስማት በውስጣቸው በትክክል አካትቷል። እነዚህ የማህበራዊ ሚዲያ መድረኮቹ የተጠቃሚዎችን የይዘት ፍጆታ (Content Consumption) በማጥናት ለረጂም ጊዜ በመድረኮቹ እንዲቆዩ በማድረግ በተጠቃሚዎች አስተሳሰብ እና ባህሪያት ላይ በዘዴ ተጽዕኖ ያሳድራሉ። እነዚህ ትኩረት የሚከፋፍሉ ነገሮች ቁጥጥር ካልተደረገበት አንድ ሰው ስለ እውነታው አለም ያለውን ግንዛቤ ሊያደበዝዝ ይችላል፣ ፍርሃትን፣ ጭንቀትን ወይም አላስፈላጊ የውስጥ-ብጥብጥ ይፈጥራል።
በእስልምና እና ክርስትና አስተምሮት ውስጥ ለእግዚአብሔር ትኩረት መስጠት የራስን ንቃተ ህሊና መጠበቂያ ብቸኛ መንገድ ነው። የእግዚአብሔርን ሁሉን ማስገኘትን እና ሁሉን አዋቂነት በአምዕሮ ማስተንተን (ሜዲቴት ማድረግ) የዲያብሎስን ትኩረትን የሚከፋፍሉ ዘዴዎችን መመከትን ያካትታል። ልክ እንደ ድርጅቾት ሁሉ ዲያብሎስም ትኩረትን በሚከፋፍሉ ነገሮች (ማስታወቂያዎች) ግለሰቦችን ከመለኮታዊ መንገዳቸው ለማራቅ ይጥራል።
የጊዜ ኃይል
እጅግ በጣም ብዙ ትኩረት የሚከፋፍሉ ነገሮች ያሉት ዘመናዊው ህብረተሰብ፣ ብዙውን ጊዜ የማያቋርጥ የአእምሮ እዣት ውስጥ ይገባል።ሰዎች መጸዳጃ ቤት እንኳን ተንቀሳቃሽ ስልኮቻቸውን ይዘው ነው የሚገቡት፤ በዲጂታል የህይወት ቅንጥቦች ውስጥ እራሳቸውን በማጥለቅ የህይወታቸውን እያንዳንዷን ቅጽበት ሳይኖሯት ያልፋሉ። ስለዚህ ተግባራቸውም ሲጠየቁ ዘና፣ፈታ እያሉ እንደሆነ ይመሰክራሉ። ነገር ግን እውነተኛ ዘና ማለት የመምረጥ አቅም ነው። እውነተኛ ዘና ማለት ከሃውለ ንፋሱ ጋራ መወላወል አይደለም። እውነት ማህበራዊ ሚዲያ ላይ የምታሳልፈው ጊዜ የመረጥከውን ያክል ነው? ወይስ መስተፋቅር እንደተሰራበት ሰው ያለምርጫ ጣቶችህ የስልክህን መስኮት እየጠረጉ ነው? መልሱን እኔም አንተም እናውቀዋለን።
የአስተሳሰብ ጥሞናን ማግኘት ጊዜን በጊዜ ሂደት መቆጣጠርን ይጠይቃል። ጊዜ፣ እንደ ጽንሰ-ሃሳብ፣ ወደ ሁለት ትኩረት የሚከፋፍሉ ነገሮች ሊመራን ይችላል – አንደኛው ‘ሀዘን’ ሲሆን፣ ትርጎሙም በትላንት ውስጥ መኖር ማለት ነው። ሁለተኛው ደግሞ ‘ጭንቀት/ውጥረት’ ነው፣ አንድ ሰው ስለወደፊቱ ክስተቶች ሲጨነቅ፤ ነጌን ካልተቆጣጠርኩት ሲል ማለት ነው።እነኚ ሁለቱ የጊዜ ግዛቶች በአሁኑ ቅጽበት ላይ ሙሉ በሙሉ የመኖር ችሎታችንን ያደናቅፋሉ።
ጊዜ የሚዳሰስ ወይም የሚታይ አይደለም። ነገር ግን ጉልህ የሆነ ኃይል ይይዛል። በአግባቡ ጥቅም ላይ ካልዋለ, ጊዜ ገዳይ በሽታ ነው። አንዳንድ ሰዎች ’ጊዜን እ፟ንግደል’ ስሉ ስሰማ ያሳዝነኛል። እነኜ ሰዎች በግልጽ በጊዜ እየተገደሉ ያሉ ሰዎች ስለመሆናቸው ምንም ጥርጥር የለውም። ነገር ግን ጊዜ በአእምሮ ጥቅም ላይ ከዋለ፣ እያንዳንዱ አፍታ አእምሯችንን እና ነፍሳችንን ወደ ጤናማ፣ ሚዛናዊ የህይወት መንገድ የምንመግብበት ውድ የፈጣሪ ስጦታ ሊሆን ይችላል። የፈጣሪን ስጦታን በፈጣሪ ላይ መልሶ ኢንቨስት ከማድረግ የበለጠ ምስጋና የለም።
እናም ውንድሜ፤ አዕምሮህን ከሚረብሹ ኃይሎች ለመራቅ፤ ትኩረትህን ፈጣሪ ላይ አድርግ (Meditate on God)።